«የኦሮሞ ትግል ፍሬ እንዳያፈራ ትልቁ ተግዳሮት የነበረው ኦነግ ሸኔ ነው» – አቶ ታዬ ደንደኣ፣ የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ
የኦሮሞ ሕዝብ ትግል ፍሬ እንዳያፈራ ትልቁ ተግዳሮት የነበረው ኦነግ ሸኔ መሆኑን የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደኣ አስታወቁ። ህወሓት ኦነግ ሸኔን በአደባባይ እንደ ጠላት እየፈረጀ በተግባር ግን የኦሮሞን ትግል ለማክሰም እንደ መሣሪያ ይጠቀምበት እንደነበረም አመለከቱ።
አቶ ታዬ ደንደኣ በተለይ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ የኦሮሞ ሕዝብ ያካሄደው የፍትህ የእኩልነትና የነፃነት ትግል ፍሬያማ እንዳይሆን ኦነግ ሸኔ ከህወሃት ጋር የነበረው ከሕዝብ የተሰወረ ህብረት ዋንኛ ምክንያት ነው ብለዋል። ኦነግ ሸኔ የኦሮሞ ታጋዮች አንድ ወጥመድ ሆኖ ለህወሃት ሲያገለግል እንደነበርም አመልክተዋል።
ብዙዎች ኦነግ ሰፊ የሕዝብ ድጋፍ እያለው የዚህ ድርጅት ትግል ለምንድን ነው ወደፊት ገፍቶ የማይመጣው? የሚል ጥያቄ ነበራቸው። በርካታ ወጣቶች እና ምሁራን እንዲሁም መምህራንም ይሄንኑ ይጠይቁ እንደነበር አመልክተው፣ የኦነግ ትግል እውነተኛ የነፃነት ትግል ነው ብለን በማመን ትግሉን ከተቀላቀልን በኋላ ግን ኦነግ ሸኔ እና ህወሓት አብረው እንደሚሰሩ መገንዘብ ተችሏል። ኦነግ ሸኔ የህወሓት መጠቀሚያ ዕቃ መሆኑንም መረዳት ተችሏል ብለዋል።
«የኦሮሞ ሕዝብ ነፃነት ይፈልጋል (ኦሮሞ ብቻም ሳይሆን ኢትዮጵያውያንም ነፃነት ፈልገው ዋጋ ሲከፍሉ ነበር)፤ ይሄን ነፃነት ማን ያመጣልኛል ብሎ ሲያስብ ደግሞ አንድ በነፃነት ስም የተደራጀ ድርጅት አለ ብሎ በማመን የትግሉ አካል ይሆን ነበር። ይሄ ድርጅት ግን ጭንቅላቱ በህወሓት በመያዙ እና ይህንን ሕዝቡ በሚገባ ባለማወቁ ብዙ ዋጋ ከፍሏል ሲሉ አስታውቀዋል።
«ህወሓት ኦነግ ሸኔን ሆን ብሎ በዚያ ደረጃ የኦሮሞ ሕዝብ፣ የኦሮሞ ወጣት፣ የኦሮሞ ምሑር የሌለ ነገር እንዲጠብቅ፤ በሴራ ያስቀመጠው ድርጅት ነው» ያሉት አቶ ታዬ፣ በዚህ መልኩም ለሃያ ዓመታት ያህል ተጠቅመውበታል፤ በተለይም አቶ ገላሳ ዲልቦ ከሥልጣን ወርደው የአሁኑ የሸኔ ሊቀመንበር ሥልጣን ከያዘ በኋላ በቀጥታ ትብብሩ ውስጥ እንደነበሩም አመልክተዋል።
«ኦህዴድ ውስጥ ሆነህ ኦሮሞ ላይ ጉዳት ደርሷል ብለህ ካነሳህ ኦነግ ትባላለህ። የኦሮሞ ባለሀብት ሆነህ ሊዘርፉህ ከፈለጉ ኦነግ ይሉሃል። ይሄን የሚያደርጉት ደግሞ ኦነግ የሌለ ከሆነ የሚፈርጁበት ስለሌለ ስለሚቸገሩ ነው። ስለዚህ ኦነግ እንደሌለና በእነርሱ ስር እንዳለ ቢያውቁትም፤ በኦነግ ስም ተማሪን ለመደብደብም፣ መምህራንን ለማሰርም፣ ነገ ይገዳደረኛል ብሎ የሚያስቡትን ለመግደልም ይጠቀሙበታል፤ ህወሓት በዚያ ደረጃ በኦነግ ሸኔ ተጠቅሟል ሲሉም ተናግረዋል።
ከዚያም በላይ ኦነግ ሸኔ የኦሮሞ ታጋዮች አንድ ወጥመድ ሆኖ አገልግሏል የሚሉት አቶ ታዬ ደንደኣ ፣ ለምሳሌ እኔ ሁለት ጊዜ ታስሬያለሁ። አስር ዓመት እስር ቤት ቆይቻለሁ። ሁለቱንም ጊዜ ያሳሰረኝ የኦነግ ሸኔ አባል ነው። ያሳሰረኝ ኦህዴድ አይደለም፤ ህወሓትም ራሱ ፈልጎ አላገኘኝም። ለህወሓት የሰጠኝ ኦነግ ሸኔ ነው። አብረው ስለሚሰሩ በገንዘብም ይሸጡሃል። እንዲያውም አንዳንዴ አደራጅተውና የኦነግን ባንዲራ አስይዘው አሳልፈው ለህወሃት ይሰጡሃልም ብለዋል።
ለምሳሌ፣ ግርማ ጥሩነህ የሚባል የሸኔ ተወካይ 2008 አካባቢ ቦሌ ላይ 20 ሰዎችን ማህበር ብሎ በአንድ ጊዜ አደራጅቶና የኦነግ ሸኔ ባንዲራ አስቀምጦ ደህንነትን ጠርቶ አስይዟቸዋል ያሉት አቶ ታዬ፣ እናም በዚያ ደረጃ ነው በሰው የሚነግዱት ይላሉ። ከተያዝክና ከታሰርክ በኋላ ደግሞ ጀግና ታሰረ ብለው ውጪ ያሉት አባሎቻቸው በስደት እያሉ የሕዝቡን ነፃነት ከሚፈልጉ የዋሆች ላይ ገንዘብ እንደሚሰበስቡም አመልክተዋል።
ከዚያ ባሻገር እነሱ የመሸጉበት ሶሎሎ የሚባል አካባቢ አለ። እዚህ መከራ ሲያይ፤ ሲታሰርና ሲገረፍ የተቸገረ ሰው በቃ ሄጄ ታጥቄ ልታገል ብሎ ወደዚያው ይሄዳል። እዚያም ይታይና ሃሳብ ያለው ከሆነና ጀግንነት ያለው ከሆነ እዚያው ይገደላል፤ ወይ ይቃጠላል። ይሄን የሚያደርጉት ደግሞ ይህ ሰው ነገ አብዮት ሊያመጣ ይችላል ብለው ስለሚሰጉ እንደሆነም ጠቁመዋል።
እንደ አቶ ታዬ ማብራሪያ፤ ህወሓትና ኦነግ ሸኔ ከዚህም ባለፈ መረጃም የሚለዋወጡ ናቸው። ለአብነት፣ ኅብረተሰቡ ሲያምጽ የወያኔ መልስ ጥይት ነው፤ ግድያ ነው። በተለያየ ጊዜ በተማሪ ደረጃ፣ በወጣት ደረጃ፣ በ2006 ዓ.ም ከዚያም በፊት በ1998፣ በ1996 እና በተለያየ ጊዜ የተለያዩ አመጾች በተለይ በኦሮሚያ ክልል ተደርገዋል። በጣም የሚያሳዝንህ ግን በዚህ ውስጥም የሴራ ፖለቲካ እንዲታይ ሆኗል።
በሴራውም ህወሓት በአጠቃላይም የኢህአዴግ መንግሥት ንጹሃን ኦሮሞዎችን ገድሏል፤ ሰብዓዊ መብትም ተጥሷል በሚል በዓለምአቀፍ ደረጃ (በአምነስት ኢንተርናሽናል፣ ሂዩማን ራይትስ ዎችና ሌሎችም) ክስ ይቀርብበታል።
ይህ ክስ ሲቀርብ ህወሓት የሚያደርገው ነገር በእኔ ትዕዛዝ ነው ሕዝቡ ያመጸው በልና መግለጫ አውጣ ብሎ የሚያነበውን መግለጫ ጽፎ ለኦነግ ሸኔ ይልክለታል። ኦነግ ሸኔም አስመራ ላይ ሆኖ በህወሓት ተጽፎ የቀረበለትም መግለጫ ያነብባል።
የእኛ ትግል ነው ብሎ ያነበበውን የእርሱን መግለጫም እነ ቪኦኤና ዶቼቬሌ ጭምር ያስተላልፉታል። ህወሓት/ኢህአዴግ ደግሞ ይሄንን ተጠቅሞ እንቅስቃሴው የሕዝብ አልነበረም፤ የአሸባሪው ኦነግ ነው ብሎ ራሱን ለመከላከል መልስ ይሰጣል። እናም በዚህ ደረጃ በረቀቀ መልኩ ከረዥም ጊዜ ጀምሮ አብረው ሲሰሩ እንደነበርም አስታውቀዋል።
ይሄንን በደንብ ለመረዳት በኢሬቻ ጊዜ በርካታ ዜጎች ሕይወታቸው አልፏል። በተቃውሞ ጊዜም በተለይ «ግራንድ ራሊ» ተብሎ በተደረገው ትልቅ ሰልፍ የብዙ ወጣቶች ሕይወት አልፏል።
የኦሮሞ ሕዝብ በአብዲ ኢሌ እና በህወሓት ሴራ በሚሊዮን የሚቆጠር ከሶማሌ ክልል ተፈናቅሏል፤ ሞቷልም። እንግዲህ ተኩስ ቢያስፈልግ ያን ጊዜ ጀግና ወጥቶ መተኮስ ነበረበት። ወጣቱ በሰላማዊ መንገድ ወጥቶ ባዶ እጁን መንገድ ላይ ሲረግፍ ኦነግ ሸኔ የሚባለው አንድ ጥይት አይደለም ወደጠላት ወደ ሰማይ አልተኮሰም ብለዋል።
ይሁን እንጂ እነ ጌታቸው አሰፋ ከሥልጣን እንደወረዱ ጫካ ታይቶታል። ይህ ምን ማለት ነው? ትግሉ የነፃነት ነው ወይስ ፀረ ነፃነት ነው? ያኔ ሕዝቡ ለነፃነት ሲታገል የት ነበሩ? አዲስ አበባ፣ አማራ ክልል፣ ኦሮሚያ ክልል፣ ደቡብ ክልል፣ ሶማሌ ክልል ሕዝቡ መከራ ሲያይ፣ ሲገረፍ፣ በግፍ ሲረግፍና ሲገደል አንድ ጥይት ለመተኮስ እንዳልሞከሩ አመልክተዋል።
በወቅቱ ከእነርሱ ጋር የነበረ ኮሎኔል አበበ ገረሱ እንደምንም ለዚህ ሕዝብ እንድረስለትም ብለው ሲጠይቃቸው፣ አይ ኢትዮጵያን ሶሪያ አናደርጋትም፣ ተኩስ እዚያ ቢካሄድ ሶሪያ ነው የምትሆነው፤ ኅብረተሰቡ በራሱ ጊዜና በራሱ መንገድ በሰላማዊ መንገድ ቢታገል ነው የሚሻለው ነው ያሉት።
ታዲያ ትጥቅ፣ ተኩስና ግድያ ከዚያ በኋላ ለምን አስፈለገ? የሚገድሉት ደግሞ እግር የቆረጠውን፤ ያኮላሸውን፤ ጥፍር የነቀለውናና ሌላም ግፍ ያደረሰውን አይደለም። ትናንት ይሄን ያደረገው ዛሬ የእነርሱ ወዳጅ ነው። አብረው ነው የሚሰሩት። እንዲያውም ሎጀስቲክስም ስትራቴጂም ከዚያ ነው የሚቀበሉት። ስለዚህ ግንኙነታቸው ከድሮም ጀምሮ ያለ እንደነበር አመልክተዋል።
ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ማወቅ የሚገባው እና በተለይም የኦሮሞ ሕዝብ ሊነቃበት የሚገባው የኦነግ ሸኔ ፕሮፖጋንዳ የኦሮሞ ሕዝብ እንደ ጭራቅና ገዳይ እንዲታይ፤ እንደ ሰይጣን እንዲፈራ እና እንዲጠረጠር የሚያደርግ ነው ያሉት አቶ ታዬ ደንደኣ፣ የኦሮሞ ሕዝብ የተለየ ጥያቄ እንዳለው እና ኦሮሞ ከኢትዮጵያ የተለየ እንደሆነ እንጂ፤ ከሌሎች ጋር ተስማምቶ ያለ እና ተመሳሳይ ጥያቄና ችግር ያለው፣ መፍትሄውም በጋራ ብንታገልና በጋራ ብንሰራ ነው የምናገኘው፤ የሚል አስተሳሰብ እንዲመጣ እንደማይፈልግም አስታውቀዋል።
በዚህም በኦሮሞና ሶማሌ ነዋሪዎች መካከል ትንሽ እንኳን የግጦሽ ሳር ግጭት ብትፈጠር የፍረጃ ወሬን በማጋጋል ኦሮሞና ሶማሌን የሚያቃቅር፤ በተመሳሳይ በሲዳማና ኦሮሞ አዋሳኝ ላይ ትንሽ ግጭት ቢፈጠር እሱኑ አጋግሎ በኦሮሞና ሲዳማ መካከል ትልቅ ጥርጣሬ እንዲፈጠር ማድረግ ትልቁ ሥራቸው እንደሆነ ጠቁመዋል።
ራሳቸው በፈጠሩት ግርግር በቤኒሻንጉል ጉሙዝና ኦሮሚያ አካባቢዎች ጉዳት በደረሰ ጊዜ የሚጠቀማቸው ቃላት ለሌሎች ማህበረሰቦች እጅግ ፀያፍ፤ የሚያበሳጩና ግጭትና ቁርሾን የሚያባብሱም እንደነበሩ አመልክተው፣ በዚህ ደረጃ ይሄን አቃፊ እና የኢትዮጵያ ትልቅ መሠረት የሆነውን ማህበረሰብ፤ ኢትዮጵያውያንን ወዶና አፍቅሮ አብሮ ኢትዮጵያን የመሠረተ እና አብሮም ለማሳደግና ለማሻገር የሚፈልገውን ማህበረሰብ ከሌሎች ወንድሞቹ ጋር እንዳይስማማ፤ እነርሱ በሚሰሩት የፕሮፖጋንዳ ሴራ ሌሎች እንዲጠራጠሩት እየሆነ ነው ብለዋል። ይሄን ማድረግ ደግሞ የህወሓት ባህሪ መሆኑን ገልጸው፣ ይህ በራሱ የህወሓትና ኦነግ ሸኔ ግንኙነት የት ድረስ እንደሆነ የሚያሳይ እንደሆነም አስታውቀዋል።
አዲስ ዘመን ሀምሌ 14, 2012
ወንድወሰን ሽመልስ