Connect with us

የብልጽግና ምሥረታ የሕወሓት እምቢታ

የብልጽግና ምሥረታ የሕወሓት እምቢታ
Photo: Facebook

ፓለቲካ

የብልጽግና ምሥረታ የሕወሓት እምቢታ

የብልጽግና ምሥረታ የሕወሓት እምቢታ (በኃይሉ ሚዴቅሳ ፍስሃጽዮን)

ኢትዮጵያ ውስጥ 160 የፖለቲካ ድርጅቶች አሉ፡፡ ሳር ቅጠሉ ሁሉ እያወራ ያለው ግን ስለ አንድ ኢሕአዴግ ስለሚባል የፖለቲካ ድርጅት ነው፡፡ በርግጥ ይህ ፓርቲ ገዥ ፓርቲ በመሆኑ መነጋገሪያ መሆኑ የሚጠበቅ ነውው፡፡ በየወረዳው አመራሮች በታጣቂ በሚገደሉበት፣ ሰው ወጥቶ መግባት በተቸገረበት፣ ኢኮኖሚው በደቀቀበት በዚህ ወቅት፣ ሚዲያውን ለዚያውም የመንግሥትን መገናኛብዙሃን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠረው የአንድ ፓርቲ ውህደት ጉዳይ መሆኑ ያስተዛዝባል፡፡ የአገሪቱ አርሶ አደር አሁን ምርት የሚሰበስብበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ ከፍተኛ የምርት ብክነት የሚያጋጥማት ወቅት ነው፡፡ይህንን እንኳን አጀንዳ አድርጎ ስለ አርሶ አደሩ የሚያቀነቅን ፖለቲከኛ፣ ኢሕአዴግና ባለሥልጣን የለም፡፡ ሁሉም ኢሕአዴግ ተዋኸደ፣ ተዋደደ፣ ተንጋደደ ይላል! አዲዮስ ኢትዮጵያ!

ከላይ እንዳልኩት ይሄ ድርጅት ገዥ ፓርቲ ስለሆነ መነጋገሪያ መሆኑ የሚጠበቅ ነው፡፡ ግን ይህንን ያህል የአንድ ፓርቲ ጉዳይ ሞገዱን ሁሉ ይዞ መቀጠል አልነበረበትም፡፡ እኔ አቶ በኃይሉ ሚዴቅሳ ይህ ጽሁፍ ስለ ኢሕአዴግና አበልፃጊ ፓርቲ የፃፍሁት የመጨረሻው እንዲሆንልኝ እመኛለሁ፡፡

ሕወሓት ይህ ውሕደት ሕግን መርህን፣ ፖለቲካዊና ነባራዊ ሁኔታን ያገናዘበ አይደለም ብሎ ‹መንቦጫረቅ› ብሎ ካጣጣለው አንድ ወር ሊሆነው ነው፡፡ በኋላም ሥራ አስፈፃሚው የሌሎች ድርጅቶችን ሕልውና የመወሰን ሥልጣን የለውም አለ፡፡ የ8ሚሊዮኖችን ፓርቲ ሕልውና 36 ሰዎች አይወስኑም አለ፡፡ በዚህም ምክንያት የተቃውሞም ውሳኔውን አሰምቶ ወጣ፡፡ አስገራሚው ነገር መንቦጫረቅ ነው፤ አንዋኸድም ሲል ከርሞ አሁን ደግሞ ከሕዝብና አባላት ጋር ልመካከር ይላል፡፡ እስኪ መክሮ ሚደርስበትን እናያለን፡፡

ትናንት ግን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ምልጃ የላኳቸው ባለሃብቶች መቐለ ሄደው ከዶ/ር ደብረጽዮን ጋር ሲመክሩ ውለዋል፡፡ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባሳለፍነው ቅዳሜ በቤተመንግሥት የትግራይ ተወላጅ ባለሃብቶችን ሰብስበው ‹‹ከሕወሓት አስታርቁኝ፤ እርሱ የሌለበት ውሕደት የትም አይደርስም፡፡ እሄዳችሁ አማክራችሁ ስትመለሱ ደግሞ እንገናኛለን›› ብለዋቸዋል፡፡ ባለሃብቶቹ ‹‹መስመር ነው ሃይላችን፤ መርህ ነው መለያችን›› የሚለውን ሕወሓትን አሳምነው የሚመጡ ከሆነ የምንሰማው ይሆናል፡፡
የኢሕአዴግ ውሕደት የሚከናወነው አብላጫ ሕዝብ ቁጥር ካላቸው ብሔረሰቦች የሚመጡ ሰዎችን በዘላቂነት የኢትዮጵያ ገዥ አድርጎ የማስቀጠል ዓላማ ያለው ሲሆን፣ አነስተኛዎችን ደግሞ ዘላለማዊ ተገዥ አድርጎ እንደሚቀጥል በሕገ ደንቡ ላይ አስቀምጧል፡፡

እንደዚያም ሆኖ ይህንን ውሕደት ከሕወሓት ባልተናነሰ እየተቃወሙ ያሉት የኦዴፓ ሰዎች ናቸው፡፡ ትናትት የጃዋር ቴሌቭዥን እንደዘገበው ከሆነ በርካታ የኦዴፓ አመራሮች በተጠራው አስቸኳይ ስብሰባ አልተገኙም፡፡ የተገኙትም እረግጠው ወጥተዋል፡፡የድርጅቱ ጠቅላላ ጉባኤ 2500 አባላት ያሉት ቢሆኑም የተገኙት ግን ከ500 እንደማይበልጡ እየተነገረ ነው፡፡ ከነዚህ ውስጥ የድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበር ለማ መገርሳ ድርጅቱን በሚያከስመውና በሚገድለው ስብሰባ ላይ አልተገኙም፡፡ በነገራችን ላይ ከታማኝ ምንጭ እንዳረጋገጥኩት፣ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ በተወያየበትና ለውሕደት ውሳኔ ባሳለፈበት የባለፈው ቅዳሜ ስብሰባ ላይ አቶ ለማ መገርሳ የድጋፍ ድምጽ አልሰጡም፡፡ እጃቸውን በከፊል አውጥተው የታዩትም ገና ማለዳው ላይ የመወያያ አጀንዳ ሲያዝ፣ ሕወሓት ‹‹በአገራችን ከኢሕአዴግ ውሕደት በላይ፣ የሠላም እጦትና የኢኮኖሚ ድቀት ቅድሚ ሊሰጠው ይገባል እርሱ ላይ እንወያይ›› በማለቷ፣ እንወያይ አንወያይ የሚለውን ለመወሰን ሲያወጡ ነው፡፡

ከአቶ ለማ እኩል በሥራ አስፈፃሚው ላይ ድምጽ ያልሰጡት አቶ ዑመር (የእርሻ ሚኒስትሩ) ናቸው፡፡ ወ/ሮ ሙፍሪያት ካሚል ከኢሕአዴግ ውሕደት የሚበልጥ አንገብጋቢ ሥራ ስላለኝ ብለው እስካሁን ውሕደትን በሚመለከቱ ወሳኝ ጉባኤዎች ላይ አልተገኙም፡፡ የእርሳቸው ፓርቲ ውሕደትን በተመለከተ ውስጣዊ አንድነቱ ምን ደረጃ ላይ እንዳለ እንጃ!

አዴፓ ሳያቅማማ ውሕደትን ተቀብሏል፡፡ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ኢሕአዴግን ይሁን አዴፓን አለያም ጠቅላይሚኒስትር ጽ/ቤትን ማንን ወክለው እንደተገኙ ባይታወቅም የሕወሓት ሊቀመንበር ለሰጡ መግለጫ ምላሽ ለመስጠት በኢቴቪ ቀርበው ነበር፡፡

ሕወሓት ‹‹ውሕደቱን ለመፈፀም የኢሕአዴግ ምክር ቤት ሳይሆን የድርጅቶች ጉባኤ ነው መወሰን ያለበት›› ማለቱን ትክክል እንዳልሆነ የገለፁት አቶ ንጉሱ ‹‹የኢሕአዴግ ምክር ቤት በጠቅላላ ጉባኤ ውክልና ተሰጥቶታል›› በማለት መልሰው ነበር፡፡ እናም የፓርቲዎች ጉባኤ በዚህ ጉዳይ መድከም እንደማያስፈልገው ተናግረው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ሁሉም ድርጅቶች በማግስቱ ጠቅላላ ጉባኤ ከመጥራት አልተረፉም፡፡ የሐዋሳው ጉባኤ ውክልና ከሰጠ ታዲያ አሁን ጠቅላላ ጉባኤን መጥራት ለምን አስፈለገ? አቶ ንጉሱን ባገኛቸው የምጠይቃቸው ጥያቄ ነው፡፡

ምንም ሆነ ምን አሁን ዋነኛ የአገሪቱ ጉዳይ ወደ ጎን ተብሎ፣ ኑሮ ውድነትና ሠላም ማጣት ባሰቃየው ሕዝብ መሀል ዋና ጉዳያችን የኢሕአዴግ ውሕደት እንዲሆን እየተሠራብን ነው፡፡ አይ ኢሕአዴግ ሞቶ የማይሞት ፍጡር!

(ከአዘጋጁ፡-ይህ ጹሑፍ የጸሐፊውን እንጂ የድሬቲዩብን ኤዲቶሪያል አቋም አያሳይም፡፡)

Click to comment

More in ፓለቲካ

Trending

Advertisement News.et Ad
To Top