“ የፖለቲካ መፍትሄ የተፈለገው፣ ወታደራዊ ድል ርቆ አይደለም !! “
( ገለታ ገ/ወልድ- ድሬ ቲዩብ )
ጥቅምት 24 ቀን 2013 ለመከላከያ ሰራዊታችን ጥቁር ቀን ነበረች ፡፡ የህወሀት ኋላቀር ፖለቲከኞችና በጦሩ ውስጥ አቆጥቁጦ የነበረው ጁንታ፣ በሰሜን እዝ ላይ አድብቶ ጥቃት የፈፀመበት የታሪክ ጠባሳ ክፉ ቀን ፡፡
ፅንፈኞች ሰራዊቱ ለትግራይ ህዝብና አካባቢው ያለውን አጋርነትና አስተዋፅኦ ክደው፣በተለያዬ ምክንያትና ሴራ ከትጥቁ እንዲርቅ አድርገው ፣ አንዳንዱ “አገር ሰላም“ ብሎ በተኛበት የፈፀሙት ክህደት በየትም አለም ያልተለመደና ወገን ከሚባል ኃይል የማይጠበቅ ወንጀል እንደነበር ተደጋግሞ ተብሏል ፡፡
ድርጊቱ ግን መላውን ሰራዊታችንን እጅግ ያስቆጣ ፣ የአገሪቱን ህዝቦች ክፉኛ ያሳዘነ ብቻ ሳይሆን ፣ መንግስት ህግን ለማስከበር ለሚወስደው ማንኛውም እርምጃ ህጋዊነትን ያለበሰ (legitimate ያደረገ ) ነበር ፡፡ በዚህም ምንም እንኳን ቀላል የማይባል መሳሪያ ተዘርፎ ፣ ቁጥሩ ትንሽ ያልሆነ ጁንታ ከአዛዥነትና ከተዋጊነት ቢከዳም፣ሰራዊቱ በሚያስደንቅ ፍጥነትና ጀግንነት የጠላትን አከርካሪ በመስበር ፣የተዘረፈውን ለማስመለስና የትግራይ ህዝብን ነፃ ለማውጣት ያገደው ሃይል አልነበረም ፡፡
በአስደንጋጭ ሽንፈት የተንኮታኮተው የጁንታው ርዝራዥ ግን ወደ ሽምቅ ውጊያ ገብቶ አገር ለማድማትም ሆነ አልሞትኩም አለሁ ለማለት አልቦዘነም ፡፡ ያንኑ መከረኛ የትግራይ ህዝብ እያስገደደ ልጆቹን ወደጦርነት ማስገባቱና ስንቅ አቀባይ ማድረጉ ሳያንስ፣ ንፁሃንን ምሽግ አድርጎ “ የጎሪላ“ ውጊያ በመቀጠሉ በርካታ ንፁሃን ለከፋ ጉዳትና ሰብአዊ ቀውስ ተጋልጠዋል ፡፡
ይህም በሀሰተኛ የትግራይ አክቲቪስቶችና የዲያስፖራ አባላት ይበልጥ እየተጋነነ በመራገቡ የአለም አቀፉን ማህበረሰብ ወቀሳ አስከትሏል ፡፡
በእርግጥ ትናንትም ሆነ ዛሬ የትግራይ ህዝብ እንዲለማና ሰላሙ እንዲጠበቅ እንጂ እንዲጎዳና ዳግም ወደ ችግር እንዲገባ የሚፈልግ መንግስት የለም ፡፡ ሌላው ህዝብም ቢሆን ለተጋሩ በጎ ከመመኘት ያለፈ ነገር አይኖረውም ፡፡ “መጥፎ ካለ ጥሩ አይጠጣም “ ነውና እብሪተኛው ድርጅት ግን ህግ ተላልፎ ህዝብ ለመማገድ በመድፈሩ ይሄ ሁሉ አገራዊ ቀውስ ተከስቷል ፡፡
ገፅታችን ጨልሟል ፡፡ የምእራባዊያንን ጣልቃ የመግባት ፍላጎትም አንሯል ፡፡
እናም ኃላፊነት እንደሚሰማው መንግስት ብቻ ሳይሆን እንደአሁኑ ትውልድ ስልጡን አተያይ ሲታይ “በእልህ ምልጭ ያስውጣል “ እሳቤ የቀውስን ጊዜ ማራዘም አይገባም ፡፡ ላድርግ ቢባልም ተደራራቢ ኪሳራ የሚያስከትል ፣በአለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚያስወግዝ መሆኑ ብቻ ሳይሆን የትግራይ ህዝብን ክፉኛ የሚጎዳ ስለሆነ በስምምነት ተኩስ አቁም መደረጉና ወደፖለቲካዊ የህግ ማስከበር እርምጃ መገባቱ የተሸለ ነው ፡፡ሊጠላም አይገባም ፡፡
ምክንያቱም ጦርነት ጎጂና አጥፊ ነው፡፡ ባለፉት ስድስት ወራት በትግራይ ውጊያ ብዞዎች ሞተዋል ፣ቆስለዋል ፣ተፈናቅለዋል ፣አካላዊና ስነልቦናዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል ፡፡ ከዚያም ከዚህም በቢሊዮን ብሮች የሚገመት የአገር ሀብትና ንብረት ወድሟል ፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ገና ላለቀው የመልሶ ማልማትና የሰብአዊ እርዳታ የመንግስትን ሩብ ያህሉን የአመት በጀት በልቷል፡፡
ይህ ሁሉ ችግር የተጠነሰሰው በጁንታዉ መሆኑ ባይካድም የተጎዳችው ግን አገርችንና ህዝቦቿ ናቸው ፡፡
እርግጥ ህወሀት እንደ ድርጅት የደረሰበት ጉዳትም የገዘፈ ነው፡፡ “በፊት ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ ” እንደሚባለው ቢሆንም፣ በርካታ የጁንታው አዛዦችና የፖለቲካ መሪዎች ሙት ፣ቁስለኛ ፣ እስረኛ ሆነዋል ፡፡አሁን በከበሮ ሞራል ለመገንባት ቢሞከርም ፣ ቀላል ግምት የማይሰጠው ወጣትና ተዋጊያቸው፣ በተቆጣ ብሄራዊ ጦር ተለብልቧል፡፡ ነገ በታሪክም እነሱ በለኮሱት ጦርነት ለተሰው የመከላከያ ሰራዊት አባላትም ተወቃሽና ተከሳሽ ፣መሆናቸው አይቀሬ ነው ፡፡
ሲጠቃለል ጦርነቱ መቆሙና ሌላ አማራጭ መፈለጉ በጎ ሆኖ ነገ ሂሳብ ለማወራረድ በሚል ሌላ ቀውስና የእርስበርስ ጦርነት የማያስነሳ መሆኑ ግን መረጋጋጥ አለበት ፡፡ ከህወሀትም ሆነ የጁንታው ባህሪ አንፃር አዘናግቶ ሌላ ጉዳትና መዳፈር አለማድረሱም መረጋጋጥ አለበት ፡፡ ከሁሉ በላይ በየጢሻው የወደቁ ጀግኖቻችን ተገቢውን ክብር እንዲያገኙና መላው ሰራዊታችንም ሞራሉ እንዲጠበቀ መደረግ አለበት ፡፡
ፖለቲካዊ መፍትሄ የተፈለገው ግን በወታደራዊ መስክ ድል ጠፍቶ ወይም ጁንታው እንደሚለው ከመቃብር ተነስቶ እንዳልሆነ ጠንቅቀን እናውቃለን !!