በጠንካራ የኦዲት ሪፖርታቸው የሚታወቁት የፌዴራል ዋና ኦዲተር ሥራቸውን ለቀቁ
ላለፉት 12 ዓመታት በዋና ኦዲተርነት ያገለገሉትና ግልፅና ደፈር ያለ ሪፖርት በማቅረብ እንዲሁም የመንግስት በጀት ከህግና ከስርዓት ውጪ ሥራ ላይ የሚያውሉ አመራሮች እንዲጠየቁ በመወትወት የሚታወቁት ዋና ኦዲተር ገመቹ ዱቢሶ ከስራቸው ለቀቁ።
ተቋሙ ባሰራጨው ዜና እንደጠቆመው አቶ ገመቹ የለቀቁት የስራ ጊዜያቸውን በማጠናቀቃቸው ነው። የፌዴራል ዋና ኦዲተር አቶ ገመቹ ዱቢሶ ከሥራ መልቀቅ በማስመልከት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት እንዲሁም የመ/ቤቱ አመራሮችና ሠራተኞች በተገኙበት መጋቢት 17 ቀን 2013 ዓ.ም የክብር አሸኛኘትና ምስጋና ተደርጎላቸዋል፡፡
በዕለቱ በተካሄተደው የሽኝትና የምስጋና መርሀ ግብር ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የመ/ቤቱ የኦዲት ዘርፍ ምክትል ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት ዳምጤ አቶ ገመቹ ዱቢሶ እና ክብረት ወ/ሮ ባዩሽ ተስፋዬ በመ/ቤቱ ቆይታቸው ሀገራቸውን እና ህዝባቸውን በላቀ የኃላፊነት ስሜት ከማገልገል ባለፈ መ/ቤቱን አሁን ለደረሰበት የስኬት ደረጃ እንዲበቃ ያደረጉ በመሆኑ በተቋሙ ታሪክ ጭምር ይታወሳሉ ብለዋል፡፡
አቶ ገመቹ ወደ ተቋሙ ሲመጡ በዓመት 32 በመቶ የነበረው የፋይናሺያል ኦዲት ሽፋን በተሰራው ጥረት የታከለበት ጠንካራ አሠራር 100% መድረሱን እና የክዋኔ ኦዲትም በዓመት በአማካይ ከነበረበት 2 የኦዲት አፈጻጸም ሽፋኑን በፍጥነት በማሳደግ ወደ 24 እንዲሁም የክትትል ኦዲት አፈጻጸምን ወደ 6 ማድረስ መቻሉን ያብራሩት ወ/ሮ መሠረት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኦዲት ለማድረግ የሚያስችል የሙከራ ስራ መጀመሩንም በንግግራቸው ጠቅሰዋል፡፡
መ/ቤቱም በአፍሪካ ካሉ ዋና ኦዲተር መ/ቤቶች አንዱ እንዲሆንና ሀገሪቱ የምስራቅ አፍሪካ አቻ የኦዲት ተቋማት አባል እንድትሆን በርካታ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን ጨምረው የገለጹት ወ/ሮ መሠረት በተቋሙ ዓለም አቀፍ የኦዲት ስታንዳርድን መሠረት ያደረገ የአሠራር ሥርዓትና ማኑዋል እንዲተገበር፣ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ግንባታን በማጠናከር የወረቀት አልባ የመረጃ መለዋወጫ ቴክኖሎጂ ተፈጻሚ እንዲሆንና ምቹ የሥራ አከባቢ እንዲፈጠር ከማስቻል ባለፈም ተቋሙ ከውጫዊ ተጽዕኖዎች ነጻ ሆኖ ሙያዊ ሥራ እንዲሠራ አመራሮቹ ያላሰለሰ ጥረት ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ መሐመድ የሱፍ በበኩላቸው የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት በሥራው በምክር ቤቱ ከየትኛውም ተቋም የተለየና የተሻለ ቦታ የሚሰጠው መሆኑን አውስተዋል፡፡
ምክር ቤቱ ግልጽነትንና ተጠያቂነትን ለማስፈን በሚያደርገው ጥረት ውስጥ መ/ቤቱ የሚያከናውነው ጠንካራ የኦዲት አሠራር ለፓርላማውም ሆነ ለቋሚ ኮሚቴው ትልቅ አቅም የፈጠረ መሆኑን አክለው የጠቀሱት አቶ መሐመድ ለዚህ ደረጃ መድረስ የአቶ ገመቹ ዱቢሶ እና የክብርት ወ/ሮ ባዩሽ ተስፋዬ ሚና የጎላ ነበር ብለዋል፡፡
በሽኝት መርሃ-ግብሩ የተገኙ የተቋሙ ሠራተኞች በሰጡት አስተያየትም ከሁለቱ የሥራ ኃላፊዎች ጋር የመስራት ዕድሉን በማግኘታቸው ደስተኞች እንደነበሩ እና በቆይታቸውም መልካምና ጠንካራ የሥራ ባህልን እንዲያዳብሩ፣ተቋማቸውን እና ሀገራቸውን ወደው እንዲሠሩ እንዳደረጓቸው ምስክርነታቸውን ሰጥተው አመራሮቹ ሁሉንም የተቋሙ ሠራተኞች በእኩል በማየትና በማስተባበር መ/ቤቱን አሁን ለደረሰበት ደረጃ ያደረሱ በመሆናቸው ወደ ፊት መልካም ዕድል እንዲገጥማቸው ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡
የአፍሪካ እንግሊዝኛ ተናጋሪ ዋና አዲተር መ/ቤቶች ማህበር (AFROSAI-E) የዋና ኦዲተር አቶ ገመቹ ዱቢሶን የዋና ኦዲተርነት የአገልግሎት ዘመን ማብቃትና ስንብት አስመልክቶ በስነ ስርዓቱ ላይ በንባብ የቀረበ መልዕክት የላከ ሲሆን ዋና ኦዲተሩ ለማህበሩ የስትራቴጂክ ዕቅድ ግብ መምታትና ለአጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴው መጎልበት ያበረከቱት አስተዋጽኦና ድጋፍ ከፍተኛ መሆኑን በመልዕክቱ ላይ በመጥቀስ ወደፊትም መልካም ዕድል እንዲገጥማቸው ምኞቱን ገልጿል፡፡
አቶ ገመቹ ዱቢሶም ለተደረገላቸው ሽኝት ምስጋናቸውን አቅርበው ዕድሉን አግኝተው ሀገርን እና ህዝብን በዚህ ደረጃ በማገልገላቸው ደስተኛ እንደነበሩ እና የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት ለሀገር ዕድገት እንዲሁም ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋፅዖ እንዲያበረክት በነበራቸው የስራ ዘመን የበኩላቸውን ጥረት ማድረጋቸውን ገልጸው ከመ/ቤቱ አመራርና መላው ሰራተኞች እንዲሁም ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ስለተደረገላቸው የትብብር ድጋፍ አመስግነዋል፡፡
አያይዘውም ተቋሙ አሁን ካለበት ደረጃ ሳይወርድ በሀገር ዕድገት ውስጥ ቁልፍ ሚና የሚጫወት ተቋም ሆና እንዲቀጥል ሁሉም የተቋሙ ሠራተኞች በርትተው ሊሠሩ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡(የፌደራል ዋና ኦዲተር)