አሜሪካና ጀርመን በኤርትራ ላይ የሮኬት ጥቃት መሰንዘሩን አወገዙ
የትግራይ ክልል በኤርትራ ዋና ከተማ አስመራ በሚገኘው አውሮፕላን ማረፊያ አካባቢ የሮኬት ጥቃት መሰንዘሩን፣ የአሜሪካና የጀርመን መንግሥታት አወገዙ።
የትግራይ ክልል ቅዳሜ ኅዳር 4 ቀን 2013 ዓ.ም. ምሽት በአስመራ ላይ የሮኬት ጥቃት መሰንዘሩን በይፋ ያስታወቀ ሲሆን፣ የኤርትራ ጦር ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጋር በመሆን በትግራይ ላይ በተለያዩ ግንባሮች ጥቃት በመክፈቱ የተሰነዘረ የአፀፋ ጥቃት መሆኑንም አስታውቋል።
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ኃላፊ ቲቦር ናዥ፣ የሮኬት ጥቃቱን በማውገዝ ቀዳሚ ናቸው። ‹‹ሕወሓት በኤርትራ ላይ የሰነዘረው ጥቃት ተቀባይነት የሌለውና በትግራይ ያለውን ግጭት ዓለም አቀፍ የማድረግ ሙከራ በመሆኑ፣ አሜሪካ አጥብቃ ታወግዛለች፤›› ሲሉ አውግዘዋል።
አክለውም በትግራይ ያለው ግጭት ሰላማዊ ሰዎችን እንዳይጎዳ ጥንቃቄ እንዲደረግ፣ እንዲሁም ሁለቱም ወገኖች በትግራይ ያለውን የግጭት ውጥረት በማርገብ ወደ ሰላማዊ መፍትሔ እንዲመለሱ መንግሥታቸው በድጋሚ እንደሚያሳስብ ገልጸዋል።
የጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ክሪስቶፈር ቡርገር በበኩላቸው፣ የትግራይ ክልልን የሚመራው ሕወሓት በአስመራ ላይ ጥቃት በመሰንዘር በትግራይ ያለውን ግጭት ለማስፋትና የጎረቤት አገሮችን ጎትቶ ለማስገባት ያደረገው ሙከራ እንደሆነ በመግለጽ አውግዘዋል።
ቃል አቀባዩ አክለው፣ ‹‹በአማራ ክልል በሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎችና በኤርትራ የተፈጸሙ ሕወሓት ኃላፊነት የወሰደባቸውን ጥቃቶች ጀርመን አጥብቃ ታወግዛለች። በትግራይ ያለውን ሁኔታ ለማረጋጋትና መፍትሔ ለማበጀት ፖለቲካዊ ሒደት ያስፈልጋል፤›› ብለዋል።
የትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) ወደ ኤርትራ ዋና ከተማ አስመራ ሮኬት መተኮሱን በይፋ አረጋግጠዋል፡፡ በምክንያትነትም የኤርትራ ጦር በተለያዩ ግንባሮች ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጋር ተሠልፎ እያጠቃ መሆኑን ተናግረዋል።
የኤርትራ ጦር ጣልቃ መግባቱን እስካላቆመ ድረስ ተጨማሪ ተመሳሳይ ጥቃቶች በኤርትራ ላይ እንደሚሰነዘሩም አስጠንቅቀዋል።
የትግራይ ጦር ከኤርትራ በተጨማሪ በባህር ዳርና በጎንደር አውሮፕላን ማረፊያዎች ላይም ተመሳሳይ የሮኬት ጥቃት የፈጸመ ሲሆን፣ በዚህም መጠነኛ ጉዳት መድረሱን የፌዴራል መንግሥት አስታውቋል።
ወደ ኤርትራ የተተኮሱት ሮኬቶች ያነጣጠሩት በአስመራ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ እንደሆነ ቢገለጽም፣ በኤርትራ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በአውሮፕላን ማረፊያው ላይ ጉዳት መድረሱን የሚያመለክቱ ነገሮች እንደሌሉ፣ ነገር ግን ከአውሮፕላን ማረፊያው አቅራቢያ ፍንዳታዎች እንደነበሩ የሚገልጹ መረጃዎች መኖራቸውን በድረ ገጹ አስታውቋል።(ዮሐንስ አንበርብር ~ ሪፖርተር)