‹የማልስማማባቸው ነገሮች በመኖራቸው ከቦርዱ ለመልቀቅ ወስኛለሁ›› ጌታሁን ካሳ (ዶ/ር) የምርጫ ቦርድ አባል
ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሥራ አመራር ቦርድ አባልነት ለመልቀቅ ጥያቄ ያቀረቡት ጌታሁን ካሳ (ዶ/ር)፣ ‹‹የማልስማማባቸው ነገሮች በመኖራቸው ከቦርዱ ለመልቀቅ ወስኛለሁ፤›› በማለት መልቀቂያ ማቅረባቸውን ተናገሩ።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በበኩሉ የቦርድ አባሉ ጌታሁን (ዶ/ር) በገዛ ፈቃዳቸው ከኃላፊነታቸው ለመልቀቅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኞ መስከረም 18 ቀን 2013 ዓ.ም. ጥያቄ ማቅረባቸውን፣ በማኅበራዊ የትስስር ገጹ ይፋ አድርጓል።
የቦርድ አባሉ መልቀቂያ ማቅረባቸውን በመጀመርያ ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሲሆን፣ ይህንን መረጃ ተከትሎም ሪፖርተር የቦርድ አባሉ ጌታሁን (ዶ/ር) መልቀቂያ ለማቅረብ የገፋቸው ምክንያት ይኖር እንደሆነ ጥያቄ አቅርቦላቸዋል። ከኃላፊነት ለመልቀቅ ካሰቡ ከአንድ ወር በላይ እንደሆናቸው ገልጸው፣ ‹‹የማልስማማባቸው ነገሮች በመኖራቸው የመልቀቂያ ጥያቄ አቅርቤያለሁ›› ብለዋል።
የማይስማሙባቸው ጉዳዮች ምን እንደሆኑ ከመናገር የተቆጠቡ ሲሆን፣ የመልቀቂያ ጥያቄው ውሳኔ ካገኘ በኋላ ምክንያቶቻቸውን ሊገልጹ እንደሚችሉ ግን ጠቁመዋል።
የቦርድ አባሉ ከኃላፊነት ለመልቀቅ መወሰናቸውን በመግለጽ ጥያቄያቸውን ያቀረቡት፣ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሥራ አመራር ቦርድ አባል አድርጎ ለሾማቸው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሆነ ገልጸዋል።
‹‹የማልስማማባቸው ነገሮች›› ያሉትን በተመለከተ፣ በሥራ ቆይታቸው ወቅት የተፈጠሩ አለመግባባቶች ይኖሩ እንደሆነ ለማወቅ የምርጫ ቦርድ የኮሙዩኒኬሽን አማካሪ ለሆኑት ሶሊያና ሽመልስ ሪፖርተር ላቀረበው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ የቦርድ አባሉ ባቀረቡት መልቀቂያ ላይ በገዛ ፈቃዳቸው ለመልቀቅ መወሰናቸውን ጠቅሰው መግለጻቸውን ብቻ እንደሚያውቁ ገልጸዋል።
የቦርድ ስብሰባዎችን እንደማይካፈሉ የገለጹት ሶሊያና፣ የቦርድ አባሉ በሥራ ወቅት የገጠማቸውና በግልጽ የጠቀሱት አለመግባባት ካለ ግን የቦርድ ስብሰባ ቃለ ጉባዔዎችን ተመልክተውና የቦርድ አባላቱን አነጋግረው ምላሽ ሊሰጡበት እንደሚችሉ አስረድተዋል።
መልቀቂያ ባቀረቡት የቦርድ አባል ምትክ ሌላ እንዲሾም ምርጫ ቦርድ ጥያቄ አቅርቦ እንደሆነ የተጠየቁት የኮሙዩኒኬሽን አማካሪዋ፣ ጉዳዩ የሚመለከተው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን እንደሆነና ምክር ቤቱም ምርጫ ቦርድን ባቋቋመበት አዋጅ ቁጥር 1133 /2011 መሠረት እንደሚወስን ገልጸዋል።
የቦርዱ ማቋቋሚያ አዋጅ አንቀጽ 12(3) ድንጋጌ መሠረት፣ የሥራ አመራር ቦርድ አባል በራሱ ፈቃድ ሥራውን ከለቀቀ ወይም በሕዝብ ተወካዮች ምክርቤት፣ በሕመም ምክንያት ተግባሩን በተገቢው ሁኔታ ማከናወን አለመቻሉ፣ ግልጽ በሆነ የሥራ ችሎታ ወይም ብቃት ማነስ፣ ከባድ የሥነ ምግባር ጉድለት መኖር፣ ወይም ለተከታታይ ስድስት ወራት በሥራ ገበታ ላይ ባለመገኘት ምክንያት ካልተሰናበተ በቀር ከኃላፊነቱ አይነሳም።
የዚሁ አንቀጽ ቀጣይ ድንጋጌ የቦርድ አባል ከቦርድ ኃላፊነቱ በፈቃዱ ከለቀቀ ወይም ጊዜውን ጨርሶ ከተሰናበተ በኋላ ባሉት ሁለት ዓመታት ውስጥ፣ በማንኛውም ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊነት ሊሾም እንደማይችል የሚደነግግ ቢሆንም በዚህ ምክንያት የቦርድ አባላቱ ብዛት ቢጓደል ምን እንደሚደረግ የሚለው ነገር የለም።
ነገር ግን የሥራ አመራር ቦርድ አባላቱን የስብሰባ ሥነ ሥርዓት የሚያስቀምጠው አንቀጽ 11 ላይ ከተቀመጠው ድንጋጌ መረዳት የሚቻለው ደግሞ፣ ከአምስቱ የሥራ አመራር ቦርዱ አባላት መካከል ሦስቱ ከተገኙ ምልዓተ ጉባዔው እንደተሟላ ይቆጠራል።
በመሆኑም መልቀቂያ ባቀረቡት የቦርድ አባል ምትክ ሌላ የቦርድ አባል አለመሾሙ፣ ቦርዱ ተግባራቱን እንዳያከናውን የሕግ እክል ይሆንበታል ማለት እንዳልሆነ ከድንጋጌው መገንዘብ ይቻላል።
በቦርዱ ማቋቋሚያ አዋጅ መሠረት የሚቋቋም ገለልተኛ ኮሚቴ በአዋጁ የተቀመጡትን መሥፈርቶች መሠረት በማድረግ በተጓደሉ አባላት ምትክ ዕጩዎችን መልምሎ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚያቀርብ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩም በቀረቡለት ዕጩዎች ላይ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ተመካክሮ የሚመርጠውን ዕጩ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በማቅረብ እንደሚያሾም አዋጁ ይደነግጋል። (ዮሐንስ አንበርብር ~ ሪፖርተር)