Connect with us

የዓባይ ፖለቲካ እና የግብጽ አሻጥር

የዓባይ ፖለቲካ እና የግብጽ አሻጥር
Egyptian President Abdel Fattah el-Sisi attends the funeral of former President Hosni Mubarak east of Cairo, Egypt February 26, 2020. REUTERS/Amr Abdallah Dalsh

ትንታኔ

የዓባይ ፖለቲካ እና የግብጽ አሻጥር

በሰው ልጆች የቀደመ ስልጣኔ ውስጥ ዓባይ ፊት መስመር ላይ ይመጣል:: ስልጣኔዎች ሁሉ በብዛት በውሀማ አካላት አካባቢ ነው የተጀመሩት፤ ከግሽ ዓባይ እስከ ሜዲትራኒያን በሚዘልቅ መንገዱ ውስጥም ዓባይ አይተኬ ሚና ተጫውቷል::

ዓባይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ 40 ከመቶውን የአፍሪካ ሀገራት በተለያየ መንገድ ሲያዋስን፤ 20 ከመቶው አፍሪካውያን ደግሞ በዓባይ ተፋሰስ ዙሪያ የሰፈሩ እንደሆኑ መረጃዎች ይጠቁማሉ:: አስራ ሁለት ያህል የአፍሪካ ሀገራት በቀጥታ ዓባይን ቢጋሩትም፤ የሚጠቀሙበት ግብጽ እና ሱዳን ብቻ ናቸው:: ከሱዳንም በላይ ደግሞ ግብጽ የተፋሰሱ አለቃ ሆና የቆመች ይመስላል::

በዚህ ሂደት ውስጥ የላይኛው ተፋሰስ ሀገራት /ኬኒያ፣ ዩጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣…/ ዓባይ በመሬታቸው ላይ ያልፋል እንጂ አይጠቀሙበትም:: እስከ 1959 እ.ኤ.አ ባለው ዘመን ዓባይ በብቸኝነት የግብጽ ፀጋ ሆኖ በቅኝ ግዛት ውሎች ታቅፎ ነበር::

ሱዳን እንኳን በ1929 እ.ኤ.አ እንግሊዝ አርቅቃ ራሷ በፈረመችው ውል ተጠቃሚ አልነበረችም:: እንግሊዝ የቅኝ ግዛት ዱካዋን ስታሰምር ከስዊዝ ካናል ጀምራ ዓባይ ከምንጩ የሚጠናቀቅ ነበር:: ወደ መካከለኛው ምስራቅ እና አረብ ሀገራት ለማለፍ ግብጽን እንደ ማለፊያ ለመጠቀም አውሮፓውያን ግብጽን ይመርጣሉ:: እንግሊዝም በቅኝ ግዛት ዘመኗ አባይን ለግብጽ በመስጠት በግብጽ በኩል የቅኝ ግዛት እጇን ለማርዘም ሞክራለች:: በታሪክ ፊትም አውሮፓውያን ግብጽን የናይል ስጦታ እያሉ ይጠሯት ስለነበር፤ በግብፃውያን በኩል የኔነት ስሜቱ አድጓል::

ግብጽ እና የሀይል አሰላለፏ
በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ዘርፍ መምህር የሆኑት አቶ ጥሩነህ አበበ ግብጽ ከአሸነፈው ጋር የመሠለፍ ታሪካዊ አዝማሚያ አላት:: በቀደመው ዘመን በተለይም በ18ኛው እና 19ኛው መቶ ክፍለ ዘመናት በወቅቱ ፈርጣማ ከነበረችው ከእንግሊዝ ጋር አብራ የቀጠናው ሀገራት ቅኝ እንዲገዙ አድርጋለች:: በዓባይ ወንዝ ላይም የላይኛው ተፋሰስ ሀገራት ውሀ እንዳይጠቀሙ አሳግዳለች::

በ2003 ዓ.ም ኢትዮጵያ በራሷ ጥረት ለመገንባት የወጠነችውን ግድብም እንዳይገነባ ከምዕራባውያን ጋር አብራ ብድር ማስከልከል ችላለች:: በ1950ዎቹ ገደማ የሶሻሊዝም አብዮት ዓለምን በሁለት ጐራ ከፍሎ በቀዝቃዛው ጦርነት ሲከታት፤ ግብጽ በታላቋ ሶቭየት ህብረት በኩል ተሰልፋ የአስዋን ግድብን አስገድባለች::

አሜሪካ በሩሲያ ተቃርኖ ላይ የቆመች ሀገር ስለሆነች የኢትዮጵያን ጥቅም ለማስጠበቅ በወቅቱ ሞክራ ነበር:: ነገር ግን የዓለም የኃይል አሰላለፍ መቀያየሩ እና በሀገር ውስጥ ያለው ፖለቲካ መርጋት አለመቻሉ የቀዳማዊ ኃይለስላሴ የአባይ ፕሮጀክት እውን ሳይሆን እንደቀረ ጋዜጠኛ ስለአባት ማናየ የአባይ ጉዳይን በቃኘበት መጽሀፍ አትቷል:: ጋዜጠኛ ስለአባት ግብጽውያን በየትኛውም ዘመን እና ሁኔታ፣ በተለየ የፖለቲካ ርዕዮት ዓለም ይሁኑ የዓባይ ጉዳይ የመቼም አጀንዳቸው ነው ሲል የግብጽን አቋም ይገልፃል::
አቶ ጥሩነህ አበበ ደግሞ ‹‹ግብጽ የአረብ ሊግ ሲፋፋም የአረብ ሊግነቷን ታስቀድማለች:: የአፍሪካ ህብረት ከአረብ ሊግ በላይ የተሻለ ተቀባይነት ሲኖረው ደግሞ ወደ አፍሪካ ህብረት ታመራለች::›› የአሰላለፏን ሁኔታ ይተነትናሉ::

ፖለቲካዊ እግሯን በተለያየ አሰላለፍ መትከሏ ለድርድር እና ውሳኔ አስቸጋሪ ሆኖ ቆይቷል ይላሉ አቶ ጥሩነህ::አሁን ላይ ግን ድርድሩ በአፍሪካውያን መደረጉን ለተፋሰሱ አባል ሀገራት የራስን ችግር በራስ የመፍታት ልምድን የሚያዳብር ሁነት አድርገው ይወስዱታል::

አቶ ጥሩነህ ግብጽ ከቀይ ባህር እስከ ሜዲትራኒያን የመሰሉ ውሃማ አካላትን ብትዋሰንም፤ የከረሰ ምድር ውሀ ሁሉ ያላት ቢሆንም አባይ ላይ ብቻ ቆማ ሌላው እንዳይጠቀም መከልከሏን በኢ-ሞራላዊ ድርጊትነት ይወስዳሉ::

በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ረዳት ፀሀፊ የሆኑት አምባሳደር ሂሩት ገብረሰላሴ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እንደተናገሩት ‹‹የኢትዮጵያ ምርኩዝ የአፍሪካ ህብረት ነው::›› ሲሉ በአፍሪካ የመዳኘትን አግባብነት ያወሳሉ:: በአፍሪካ ህብረት መዳኘት እና ኢትዮጵያውያን አንድነታቸውን ማጠናከር የማሸነፊያ መንገዱ እንደሆነም አምባሳደሯ አብራርተዋል::

የዓባይ ፍላጎቷ
ግብጽ በቀዳሚነት በዓባይ ላይ ማንም መጠቀም የለበትም ብላ ታስባለች:: በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውሀ ፖለቲካ ተመራማሪ እና የአባይ ጉዳይ ተደራዳሪ ፕሮፌሰር ያዕቆብ አርሳኖ እንደሚያብራሩት “ግብጽ ኢትዮጵያ አባይን መገደብ ከጀመረች፤ ሌሎቹ የላይኛው ተፋሰስ ሀገራትም ናይልን የመገደብ ሞራል ያገኛሉ” ስትል ትስጋለች ይላሉ:: ይህ ስጋት ደግሞ ብቻየን ልጠቀም ከሚል የመነጨ ይሆናል::
ምንም እንኳን በግብጽ በበጎ ባይተረጎምም፤ 74 ከመቶ የተጠናቀቀው እና በቅርቡ ሙሌቱ የተጀመረው የዓባይ ግድብ የላይኛው ተፋሰስ ሀገራት ማነቃቂያ እና ለቀጠናዊ ትስስርም አወንታዊ ሚና እንደሚኖረው ይጠበቃል::
ግብጽ ግን የኢትዮጵያን፣ ዩጋንዳን፣ የኬኒያን ፣… ተጠቃሚነት ወደ ጐን ገፍታ የምስራቅ አፍሪካ ፖለቲካ እንዳይረጋጋ በተቻለበት ሁሉ ግጭት ለመፍጠር ትንቀሳቃሳለች::
ከ100 ሚሊዮን በላይ ከሚሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ 65 ሚሊዮኑ መብራት አላገኘም:: ናይልን 86 ከመቶውን ኢትዮጵያ እያመነጨች ምንም አለመጠቀሟ ለግብጽ ግድ አልሰጣትም:: ግብጽ በአስዋን ግድብ አካባቢ ብቻ ከ10 ሚሊየን ኪዩቢክ በላይ ውሃ በትነት ታባክናለች:: ይህ የውሃ መጠን ከአዋሽ ወንዝ የውሃ ይዞታ በሶስት እጥፍ እንደሚበልጥም ፕሮፌሰር ያቆብ አርሳኖ ያስረዳሉ:: ኢትዮጵያ ግብጽ በትነት የምታጠፋውን ውሃ ያህል እንኳ መጠቀም አልቻለችም:: ይሄን የተመለከቱ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን ከጀመሩ በግድቡ ጉዳይ ኢትዮጵያ መደራደር አልነበረባትም:: ከራሷ የሚመነጭን ወንዝ ገድባ የመጠቀም መልካዓምድራዊ ፖለቲካ(ጂኦፖለቲካው) ይፈቅድለታል ይላሉ:: ኢትዮጵያ ግን ለአብሮነት እና ለቀጠናዊ ትብብር ስትል ውይይት እና ድርድር መርጣለች::
አምባሳደር ዲና ሙፍቲ አሁናዊ የኢትዮጵያ ድርድር ከሙሊቱ ጋር ቢሆንም፤ ግብጽ ግድቡን በአሳሪ ህጐች በማጠር እውን እንዳይሆን ትፈልጋለች ይላሉ:: ይህ የተለጠጠ ፍላጐቷ ለስምምነት ምቹ ባለመሆኑ የሰሞኑ ስብሰባ ያለ ውጤት ተበትኗል:: ግብጽ የግድቡን ሙሌት በማራዘም ኢትዮጵያን የማዳከም ፍላጎት ያላትም ይመስላል::
ግድቡ ከተገደበ በኋላ የአስዋን ሃይቅ በበረሃማ ወቅት ሲጎድል ኢትዮጵያ የመሙላት ግዴታ አለባት የሚል ፍላጎት አላት:: ይሄን ፍላጎቷን ደግሞ አንዴ ከጸጥታው ምክር ቤት ሌላ ጊዜ ከአሜሪካ ጋር፣ የሊጉ አውራ ነኝ ብላ ከምታስበው ከአረብ አባል ሀገራት ሆና ለማሳካት ደፋ ቀና ማለቷ አልቀረም::
ሚዲያዎቿም ኢትዮጵያ ለምትገድበው ግድብ መጥፎ ገጽታ በማላበስ እና የግብጽን የተለጠጠ ፍላጎት በማስተጋባት ዲፕሎማሲያዊ ትርፍ ለማጋበስ እየተንቀሳቀሰች ነው:: ይህ ጉዞዋ ግን ኢትዮጵያን ግድቡን ከመገደብ አልገታትም:: ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን የሰላ ዲፕሎማሲ እና ሀገራዊ አንድነት ኢትዮጵያ በእጀጉ ያስፈልጋታል:: ይህ ገቢራዊ ሲሆን የጋራ ተጠቃሚነት መርህን ባከበረ መንገድ ኢትዮጵያ ለምትገነባው ግድብ የተፋጠነ ውጤት ይገኝበታል::

(የሺሀሣብ አበራ)
በኩር ጋዜጣ ሐምሌ 13 ቀን 2012 ዓ.ም ዕትም

Continue Reading
Advertisement News.et Ad
You may also like...
Click to comment

More in ትንታኔ

Trending

Advertisement News.et Ad
To Top