ከትላንት በስቲያ ቀትር ላይ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ዋና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር_ክፍሌ ሆሮ በቴሌቭዥን መስኮት ብቅ ብለው የህዳሴ ግድብ የተርባይኖች ቁጥር ሶስቱ እንዲቀነሱ መደረጉን አምነው ግን ይህ መሆኑ ግድቡ በሚያመነጨው ኃይል ላይ የሚያመጣው ለውጥ አይኖርም” የሚል ገለጻ አደረጉ፡፡ ከዚያም ምድር ቁና ሆነች፡፡ ከግራ ከቀኝ አቧራው ጨሰ፡፡
ዛሬ ደግሞ ብቅ ያሉት ሚኒሰትር ዶ/ር ስለሺ በቀለ የግድቡ የማመጨት አቅም በአሁኑ ሰዓት 5 ሺ 150 ሜጋዋት ዝቅ ስለመደረጉ በመጠቆም በተዘዋዋሪ ግድቡ ያመነጫል ተብሎ ሲጠበቅ ከነበረው ቅናሽ መደረጉን አምነዋል፡፡
ኢንጂነር ክፍሌ ለቢቢሲ አማርኛም በሰጡት ተመሳሳይ መግለጫ እንዲህ ይላሉ፡፡ አንድ የኃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ትልቅነት የሚለካው ጄነሬተሮች ወይም ተርባይኖችን በመደርደር አይደለም፡፡ ብዙ ተርባይኖችን መደርደር ሁልጊዜም አዋጭ አይደለም፡፡. ለአንድ የኃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ቁልፍ ከሆኑት ነገሮች መካከል የመጀመሪያው ግድቡ የሚይዘው የውሃ መጠንና ውሃው ከምን ያክል ከፍታ ተወርውሮ ተርባይኑን ይመታል የሚሉት ናቸው አሉ፡፡
ጄነሬተሮች መካኒካል ኢነርጂን ወደ ኤሌክትሪካል ኢነርጂ እንደሚቀይሩ የሚያስረዱት ኢንጂነር ክፍሌ፤ “ጄነሬተር ወይም ተርባይን መደርደር በሚመነጨው የኢነርጂ (የኃይል) መጠን ላይ የሚያመጣው ለውጥ የለም” በማለት ያስረዳሉ።
ኢንጂነር ክፍሌ አያይዘውም “ተርባይን ተቀነሰ ብሎ ማውራቱ ትርጉም የለውም። ለአንድ የኃይድሮ ኃይል ማመንጫ ወሳኙ ኢነርጂ (ኃይል) ነው፡፡ በሥራ ላይ ይውላሉ ከተባሉት ከ16ቱ ተርባይኖች መካከል ሶስቱን ለመቀነስ የታሰበው ከዋጋና አዋጭነት አንፃር እንደሆነ ያስረዳሉ። ይህ ውሳኔም በምንም አይነት መልኩ ከግብጽ ፍላጎት ጋር የተገናኘ አይደለም ሲሉም ሊስረዱን ሞከሩ፡፡
ዋና ሥራ አስኪያጁ ከዝናብ መጠን ጋር ተያይዞ በየዓመቱ ግድቡ የሚይዘው የውሃ መጠን እና የውሃው የከፍታ መጠን ሊለያይ እንደሚችል በማስገንዘብ፤ የህዳሴ ግድቡ ያመነጫል ተብሎ የተሰላው በዓመት በአማካይ 15 ሺ 760 ጊጋ ዋት (Gigawatt hours) ወይም አንድ ሚሊዮን ኪሎ ዋት ሃዎር እንደሆነ ይናገራሉ።
“በዚህ የኢነርጂ (ኃይል) መጠን ላይ የተለወጠ ነገር የለም” የሚሉት ኢንጂነሩ፤ “አሁን ይህን ኢነርጂ (ኃይል) ለተጠቃሚው እንዴት ላድርስ? የሚለው ጥያቄ ሲነሳ ጄነሬተሮች ይመጣሉ” ይላሉ።
የሰውየው ንግግር ብዙዎች ሊዋጥላቸው አልቻለም፡፡ አንዳንዶች የመካድ ስሜት እንዲሰማቸውም ምክንያት ሆኗል፡፡
እውነትና ንጋት እያደር ይጠራል እንዲሉ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ተርባይኖች እንዲቀነሱ ከመደረጉ ጋር ተያይዞ ግድቡ 5 ሺ 150 ሜጋዋት እንዲመነጭ መደረጉን የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ በዛሬው ዕለት ለካቢኔ አባላት ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ማመናቸው ተሰምቷል፡፡
ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው የተርባይን ቅነሳን በተመለከተም አሁን ላይ ግድቡ 5 ሺህ 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል እንዲያመነጭ ተደርጓል ያሉት ሚኒስትሩ፤ በተርባይን ቅነሳው ላይ የግብፅ ፕሮፖዛል ጥቅም ላይ ውሏል የሚለው ሀሳብ መሰረተ ቢስ መሆኑን ነው ያነሱት፡፡
የተርባይን ቅነሳ ተግባር በዋናነት ቴኪኒካዊ ስራ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ የግድቡን ሃይል የማመንጨት አቅም የማይጎዳ መሆኑን ገልፀዋል ሰል ዋልታ ዘግቧል፡፡
ሆኖም ግድቡ ቀደም ሲል ያመነጫል ተብሎ ከታቀደው አንጻር እንዲቀንስ የተደረገው በምን ምክንያት እንደሆነ ዝርዝር ማብራሪያ ስለመስጠታቸው የተዘገበ ነገር የለም፡፡
ከዚህ ቀደም የህዳሴ ግድብ ባለሙያዎች እና ከፍተኛ አመራሮች በተደጋጋሚ ታላቁ የህዳሴ ግድቡ 16 ተርባይኖች እንዳሉት እና እያንዳንዳቸው 375 ሜጋ ዋት እንደሚያመነጩ በተደጋጋሚ ለህዝብ መነገሩ የሚታወስ ነው፡፡