Connect with us

#ሰበር_ዜና

#ሰበር_ዜና
ፎቶ:- ስዩም፣አባይ እና አስመላሽ

ዜና

#ሰበር_ዜና

#ሰበር_ዜና

ስዩም መስፍን፣ አባይ ፀሐዬ፣ አስመላሽ ወ/ስላሴ  ተደመሰሱ

~ ሌሎች  የህወሓት ከፍተኛ አመራሮችም ይገኙበታል

የመከላከያ ሰራዊት ሀይል ስምሪት መምሪያ ሀላፊ ብርጋደል ጀነራል ተስፋዬ አያሌው፣ ጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊት እና ሌሎች የፌዴራል የፀጥታ ተቋማት ዛሬም እንደ ትናንቱ አስደናቂ ጀግንነታቸውን በአንፀባራቂ ድል ታጅበው በድል መወጣት መቀጠላቸውን ለኢዜአ ገልፀዋል።

አሁንም የተቀሩትን የጁንታ አመራሮች የገቡበት ገብተው የማደን ተግባራቸውን አጠናክረው ቀጥለዋልም ብለዋል።

የጁንታው ቡድን ከትጥቅ ትግሉ ጀምሮ በስልጣን ላይ እያለ ኢትዮዽያዊ፣ ከስልጣን ሲወርድና የማይመች ሁኔታ ሲፈጠር ደግሞ አገርን የመበታተንና የማተራመስ ስትራቴጂ ነድፎ የማያሸንፈውንና የማይወጣውን ውጊያ በአባት አርበኝነት ለመፈፀም ሲንቀሳቀስ እንደቆየ ጠቁመዋል።

ከዚህ ተግባሩ ሊቆጠብም ሆነ ከትላንት ሊማር ያልቻለው የጁንታው ቡድን በሰራዊታችን ላይ ውጊያ ከፍቶ በለኮሰው እሳት በመለብለብ ላይ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።

የጁንታው ቡድን አመራሮች ባለፈው ጥቅምት መጨረሻ በመቀሌ በተካሄደው ዘመቻና ድምሰሳ ወቅት በ48 ሰዓት እጅ እንዲሰጡ ቢለመኑም፣ በማናለብኝነትና ትዕቢተኝነት እምቢ በማለት ወደ ጫካ መግባታቸውን ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ አስታውሰዋል።

በድጋሚም የአገር መከላከያ ሰራዊት የሀገር ሽማግሌ ጭምር በመላክ እጅ እንዲሰጡ፣ ትጥቅ እንዲፈቱና ጉዳዩቸው በህግ እንዲታይ ቢያስጠይቅም አሻፈረኝ ብለውና የያዙትን የጥበቃ ሀይል በመተማመን እንዲሁም “ተመልሰን እንነሳለን” በሚል የድሮ ብሂል ተሳስተው ያለ እድሜያቸው በዱር በገደሉ ተሸሽገዋል ብለዋል፤ ዋሻዎችን በመጠቀምም ከጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊታችን እይታ ውጪ ለመሆን ጥረት በማድረግ ላይ ናቸው ሲሉም ገልፀዋል።

ሆኖም ደከመኝ ሰለቸኝ የማይለው ጀግናዊ የሀገር መከላከያ ሰራዊትና ሌሎች የፌዴራል የፀጥታ ሀይሎች በዛሬው እለት በጋራ ባደረጉት ጠንካራ ፍተሻ በተከዜ ወንዝ ዳርቻ ቀደም ሲል ሰራዊቱን በማስመታት ኢትዮጵያን ለማተራመስ ሲንቀሳቀሱ፣ ሲያቅዱና ሲመሩ የነበሩ ቀንደኛ የጁንታው አመራሮች ከጥበቃ ሀይላቸው ጋር በነበረው ተኩስ ልውውጥ በውጊያ ላይ ከነጥበቃዎቻቸውና የጥበቃ ወታደራዊ አራሮቻቸው ጋር መደምሰሳቸውን ለኢዜአ ገልፀዋል።

እነዚሁ በነበረው ውጊያ ከጥበቃዎቻቸው ጋር አብረው የተደመሰሱ የጁንታው አመራሮች፣

  1. አቶ ስዩም መስፍን፣ የቀድሞው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩ እንዲሁም ውጊያውን የመሩና ሰራዊቱ ከቦታ ቦታ እንዳይንቀሳቀስ ያዘዙ፣ በመጨረሻም በሰራዊቱ ላይ ውጊያ እንዲከፈት ትዕዛዝ የሰጡ፣
  2. አቶ አስመላሽ ወልደስላሴ፣ የጁንታው ከፍተኛ የፖለቲካ አመራር የነበሩ
  3. አቶ አባይ ፀሃዬ፣ የጁንታው ከፍተኛ የፖለቲካ አመራር የነበሩ
  4. ኮሎኔል ኪሮስ ሀጎስ ከመከላከያ የከዳ ከነጥበቃዎቻቸው ተደምስሰዋል

በሌላ በኩል በቁጥጥር ስር የዋሉ ወታደራዊና የክልል አመራሮች

  1. ኮሎኔል ገብረመስቀል ገብረ ኪዳን፣ ከመከላከያ የከዳ
  2. ኮሎኔል ፍስሃ ብርሃኔ፣ ከመከላከያ የከዳ፣
  3. ኮሎኔል ዘረአብሩክ ታደሰ፣ ከመከላከያ የከዳ፣
  4. ኮማንደር ገብረኪዳን አስገዶም የልዩ ሀይል ክፍለ ጦር አዛዥ የነበረ
  5. አቶ መብራህቶም ክንዴ ሀይሉ፣ የክልሉ ውሃ ስራዎች ድርጅት ፋይናንስ ሀላፊ የነበረ በቁጥጥር ስር ውለዋል።

የመከላከያ ሰራዊት ኃይል ስምሪት መምሪያ ሀላፊ ብርጋደል ጀነራል ተስፋዬ አያሌው፣ ባስተላለፉት መልዕክት፣ አሁንም በየዋሻው የተደበቁ የጁንታው ቡድን አባላት በሰላማዊ መንገድ እጅ እንዲሰጡ ጥሪ አቅርበዋል።

“ትርጉም ለሌለው ጁንታ ጠባቂ በመሆን ውድ ህይወታቸውን አትገብሩ፣ ከቻላችሁ ይዛችኋቸው፣ ካልቻላችሁ በሰላም ለሰራዊቱ እጅ እንድትሰጡ ጥሪ አቀርባለሁ” ብለዋል።

በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ አንዳንድ የትግራይ ተወላጆች ጁንታው ተመልሶ ይመጣል በሚል ያላቸው ግምት የተሳሳተና የጁንታው ቡድን ዘመን ያከተመ መሆኑን አውቀው፣ ከሀገራቸውና ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ ሽግግር መንግስት ጎን በመሆን ትግራይን እንዲያደራጁ፣ እንዲያለሙና መላው ህዝብም የጀመረውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።(EBC)

ፎቶ:- ስዩም፣አባይ እና አስመላሽ

 

Click to comment

More in ዜና

Trending

Advertisement News.et Ad
To Top