ከኢትዮጵያዊ አባት እና ከዩክሬናዊት እናት የተወለደችው ታማራ ማርያም ዳዊት የሰራቸው ሳሊን ፍለጋ (Finding Sally.) የሚል መጠሪያ ያለው ጥናታዊ( Documentary ) ፊልም ተመርቆ በ ሲቢሲ ( Canada Broadcast Corporation ) በ ዚህ ሳምንት ለሲኒማ አፍቃሪዎች ለዕይታ ቀርቧል።
የታሪኩ ጭብጥ የ ሚያጠነጥነው በ 1969 ዓም ካናዳ ከ ሚገኘው ዝነኛው ካርለተን ዩኒቨርሲቲ በ ሶሲዮሎጂ ( Sociology )ባችለር ኦፍ አርትስ አግኝታ ወገኖችን ለ ማገልገል ወደ ኢትዮዽያ ተመልሳ በህቡዕ የሚንቀሳቀሰው የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፖርቲ( ኢህአፓ) የ ፖለቲካ ድርጅት አባል ሆና ህይወቷን ባጣችው አክስቷ ፣ሰላማዊት ዳዊት አብዲ፣ ታሪክ ላይ ያጠነጠነ ሲሆን በሲኒማው ዙሪያ በአሁኑ ወቅት ለስራ ጉዳይ በአዲስ አበባ ከተማ የምትገኘው ታማራ ከህብር ሬዲዮ ዘጋቢ ጋር በስልክ ባካሄደችው ቃለ ምልልስ ዶክመንተሪ ፊልሙ 600 ሺ የካናዳ ዶላር መፍጀቱን፣ ከእንግሊዘኛ ቋንቋ በተጨማሪ ወደ አማርኛ ቋንቋ መተርጎሙን እና በቀጣይነትም በ አፋን ኦሮሞ እና በ ትግርኛ ቋንቋ እንደሚተርጎም ውጥኗን ተናግራለች።
እንደ ዳይሬክተሯ ገለፃ “የሲኒማው አውንታዊ አስተዋጽኦ በ ኢትዮዽያ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ቀይሽብር ጥሎት የሄደው ጥቁር ታሪክ እንዳይደገም፣ የ ሴቶች ተሳትፎ በ ህቡዕ የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ የ ነበራቸውን የ ፖለቲካ ተሳትፎ እና ሚና አጉልቶ ማሳየት ነው” ብላለች።
ይህንን ታሪካዊ ዶክመንተሪ ፊልም በ አለም ዙሪያ የ ሚገኙ ኢትዮዽያዊያን እንዲመለከቱት እና ተጨማሪ ግንዛቤ እንዲያዳብሩ አዘጋጆቹ ግብዣቸውን ያስተላለፉ ሲሆን በ ተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ለሚገኘው የ ቀይ ሽብር ሰማዕታት ሙዚየም ፊልሙን እንደሚያበረክቱ ለ ህብር ዘጋቢ ነግረውታል ።
ሰላማዊት( ሳሊ) በ ተማሪዎች እንቅስቃሴ ግምባር ቀደም መሪ የ ነበረው እና የ ኢሀአፓ ወታደራዊ ክንፍ የ ነበረው የኢትዮዽያ ሕዝብ አብዮታዊ ሠራዊት ( ኢሕአሠ ) አመራር የነበረው የፀሎተ ሕዝቅያስ ባለቤት ስትሆን ፣ሳሊ በካናዳ የመጀመሪያው የኢትዮዽያ ባለ ሙሉ ሥልጣን አምባሳደር እና በ ቀ.ኃ.ሥ ዘመን ከፍተኛ መኮንን የነበሩት የብርጋዲዬር ጄነራል ዳዊት አብዲ ልጅ መሆኗን ለማወቅ ተችሏል።
(ኤልያስ አወቀ /ህብር ሬዲዮ)