Connect with us

አንዳንድ ነጥቦች ስለጠ/ሚ ዐብይ አሕመድ

አንዳንድ ነጥቦች ስለጠ/ሚ ዐብይ አሕመድ
Photo Facebook

ፓለቲካ

አንዳንድ ነጥቦች ስለጠ/ሚ ዐብይ አሕመድ

አንዳንድ ነጥቦች ስለጠ/ሚ ዐብይ አሕመድ

(ያሬድ ጥበቡ)

የኮሮና ቫይረስ ጥቃት፣ ይህም በኢትዮጵያ የምርጫ ሰሌዳ ላይ ያስከተለው መዘግየት፣ ቫይረሱ በዓለም ኢኮኖሚ ላይ ሊያሳድር የሚችለው መዳከምና ሥራአጥነት ወዘተ ለጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ ፋታም ሆነ የማሰቢያ ጊዜ የሚሰጣቸው ይመስለኛል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በዛፍ ተከላው፣ በቤተ መንግስት ማቆንጀት ሥራው፣ በእንጦጦ የሽርሸር ሥፍራ ቅየሳው፣ በሸገር ወንዝ መዝናኛ ፕሮዤያቸው ሁሉ አንድ ያሳዩን ነገር ቢኖር የተዋጣላቸው የፕሮጀክት መሪ መሆናቸውን ነው። አሁንም ኮሮናን ለመቆጣጠር የሚያካሂዱትን ሥምሪት በሩቅ ሆኜ ስታዘብ፣ ከትራምፕ እጅግ በተሻለ መንገድ እንደሚመሩት የማስብ መሆኑን ለወዳጆቼ አወራቸዋለሁ።

ሰሞኑን ሙሉውን ያላዳመጥኩት የአቦይ ስብሃት ቃለምልልስ ላይ፣ ዶክተር አቢይ “የተባበሩት መንግስታት ዋና ፀሀፊ መሆን እችላለሁ” ብለው ሲናገሩ ማድመጣቸውን በስላቅ መልክ ሲናገሩ ሰማሁ። ሆኖም ጉዳዩን ከምር ወስጄ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን አልመው ቢንቀሳቀሱ፣ በኖቤል ሽልማቱ ምክንያት በዓለም መድረክ ላይ ለመታወቅ ያገኙትን እድል በመጠቀም፣ ካለሙበት መድረስ ይችላሉ” ብዬ ማሰብ ጀምሬያለሁ።

ከአቦይ ስብሃት ስላቅ በፊት፣ የተባበሩት መንግስታት ዋና ፀሀፊ መሆን ይችላሉ ብዬ ባላስብም፣ ከዴሞክራሲያዊ ምርጫ በኋላ ለሁሉት ዙር የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ ተደራድረንና፣ የፕሬዚዳንቱን ሥልጣን እስካሁን ከቆየው የተዳከመና አፋዊ (nominal) ይዘቱ እንዲሻሻል ተቀብለን፣ አቢይ አሁን የያዙትን የፓርቲ መሪነትና የምርጫ ተወዳዳሪነት ትተው፣ በ”መደመር” እሳቤያቸው እየተመሩ ኢትዮጵያችንን ወደ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ቢመሯት የኢትዮጵያ ታላቁ የታሪክ ሰው ከመሆንም አልፈው የዓለም ታሪክ ውስጥ ይገባሉ ብዬ ያሰብኩባቸው ጊዜያት ጥቂት አልነበሩም። ጠቅላይ ሚኒስትር ከመሆናቸው በፊት የተባበሩት መንግስታት ዋና ፀሀፊ ለመሆን ፍላጎት እንደነበራቸው መናገራቸውን አሁን ማወቄ ደግሞ፣ በፊት ያሰብኩላቸው ከፓርቲ መሪነት ወጥተው የሽግግሩ ነፃ መሪና፣ ከምርጫው በኋላም የኢትዮጵያ ፕሬዚደንት መሆን፣ የዓለም መንግስታቱ መሪ ለመሆን ያላቸውን ህልም የሚያሳልጥላቸው ሆኖ ተሰምቶኛል።

ይህን ሁሉ ለማሰብ ያስገደደኝ አንድ እንደ ንጋት ፀሀይ የማይቀር መሆኑን የማውቀው ሃቅ ነው። ሽግግሩን የሚመራው ሰው የሚወዳደርበት ምርጫ ነፃ ፍትሃዊና ርቱዕ የመሆን እድሉ ዜሮ መሆኑን ህይወትም ጥናትም ስላስተማሩኝ ነው። ከብልፅግና ፓርቲ መመሥረት ወዲህ ባሉት ወራት የታዘብናቸው ፍፃሜዎችም የሚጠቁሙን ይሄንንው ነው። እመለስበታለሁ። በነገራችን ላይ፣ ይህ የአቢይ የተለየ ድክመት ሳይሆን ማንኛችንም በዚህ ሁኔታ ውስጥ ብንተው የሚገጥመን ችግር ነው። ስለሆነም መፍትሄ ይሻል።

የሺህ ዓመታት የመንግስታዊ ሥርአት ልምድና አቅም ይዘህ፣ የሚታዘዝ ሠራዊት፣ ደህንነትና ፖሊስ ከቦህ፣ ያለገደብ ልትጠቀምበት የምትችል የመንግስት ካዝና፣ ቁሳቁስና የሰው ሀይል ይዘህ በምትወዳደርበት ምርጫ ውሰጥ እንዴት መሸነፍን ትቀበላለህ? ለማሸነፍ የሚያስችሉህን ነገሮች ሁሉ ከማድረግ ወደኋላ አትልም። በዚህ ላይ በዚህ አፋኝ በነበረ ሥርአት ውስጥ በሥልጣን ላይ ለብዙ ዓመታት የቆየህ ከነበረ፣ ከቁም ሳጥን የሚወጣ አፅም ሊኖርህ ስለሚችል፣ ሥልጣንን በቀላሉ መልቀቅ አትፈልግም። ስለሆነም በእጅህ ለማቆየት ትሞክራለህ። ለዚህም ነው፣ በምርጫው ውጤት ላይ ተጠቃሚ ያልሆኑና፣ ከሽግግሩ በኋላ በሚኖረው ሥልጣን የማይሳተፉ ሰዎች ሽግግሩን ይምሩት የሚባለው። የኢትዮጵያም ሽግግር የጎደለው ትልቅ ክፍተት ይህ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩና ፓርቲያቸው የሃገሪቷን ባለሀብቶች ሰብስበው ያደረጉትን “ዝርፊያ” ማየት ነው። አቢይ ራሳቸው እንደነገሩን ባለሃብቶቹ፣ 1ቢሊዮን 300 ሚሊዮን ብር ለብልፅግና እንዲያዋጡ ተደርጓል። በውጭ ባንኮች አሽሽተው ከሚያስቀምጡት ብልፅግና እጅ መግባቱ የተሻለ ነው ብሎ የሚከራከር ይኖር ይሆናል። ሆኖም፣ መንግስታዊ ሥልጣናቸውን ተመክተው እንዲዋጣ ያደረጉት በመሆኑ፣ ከምርጫው ባሻገር መጭውን ጊዜ አመላካች በመሆኑ አስፈሪ ነው። ልጓም በሌለው ፍፁም ሥልጣን ውስጥ እንዲህ ዓይነት ብልግና የሚጠበቅ ነው። ልጓም ለመሆን ይችሉ የነበሩት ምርጫ ቦርድና የዓቃቤ ህግ ሥርአቱም፣ ፍፁም ሥልጣንን ፈርተው ዝምታን መርጠዋል። ይህም ፍፃሜ ልሙድ እየሆነ መቀጠሉም አይቀርም። በዝያው መጠንም ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርአት የመሸጋገር እድላችንም በእጅጉ እየራቀ ይሄዳል። ምርጫ ግን ያለን ይመስለኛል። በጭለማ ውስጥ መቀጠል የለብንም። ዶክተር አብይ ከራሳቸው ጋር ቁጭ ብለው ቢመክሩ ከዚህ ጨለማ ለመውጣት ሊረዱን ይችላሉ ብዬ አስባለሁ።

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ለመሆን፣ ምርጫውን ለማሸነፍ መጓዝ የጀመሩበትን መንገድ፣ የከፈሉትን መስዋእትነት፣ የምርጫው ውጤት የሚያስከትላቸውን ምስቅልቅሎች ወዘተ አስበው፣ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆኑን ትቼ ከማንኛውም ፓርቲ ነፃ ሆኜ ሽግግሩን ብመራና ኢትዮጵያን ወደመጀመሪያው ዴሞክራሲያዊ ተስፋ ባሻግራት ከማገኘው ዓለማዊ (ሉላዊ) ክብር አኳያ ሲመዘን የቱ ይበልጥብኛል ብለው ተጨንቀው ቢያስቡ ደስ ይለኛል።

የኢንቬስትመንት አማካሪዬ የእንግዳቤቱ ግድግዳ ላይ የመጀመርያው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበረው ጆርጅ ዋሽንግተን ዴላዎርን ሲያቋርጥ የሚያሳየውን ታዋቂውን ሥእል ሰቅሏል። ሥእሉ፣ የታዋቂነቱን ያህል ብዙ አቃቂር የወጣለት ነው። ይህንንም እያወቀ ነው የሰቀለው። ሰለ ሥዕሉ ለጠየቀው ሰው ሁሉ ግን “ያን ሥዕል የሰቀልኩት ህፀፅ እንዳለው ሳይገባኝ ቀርቶ ሳይሆን ትልቁን የዓለም መሪ ስለሚያሳይ ነው። ዋሽንግተን በዘመኑ ታዋቂ የነበረውን የዓለም ሃያል ጦር ተጋፍጦ፣ ያልሰለጠነ የገበሬ ሚሊሺያ ጦር መርቶ ያሸነፈና የአሜሪካን ነፃነት ያስገኘ ጄኔራል ቢሆንም፣ ኮንግረስ ፊት ቀርቦ ተልእኮዬን ፈፅሜያለሁ ጎራዴዬን ተረከቡኝ ብሎ ትጥቁን በህዝብ ምክርቤት ፊት ያወረደ ጀግና ስለነበር ከዓለም ታላላቅ መሪዎች ሰልፍ ሊቀላቀል ችሏል” ብሎ በጥልቅ ስሜት ይናገራል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ ከዚህ የዋሽንግተን ታሪክ ብዙ መማር ይችሉ ይመስለኛል። ለማሸነፍ የሚታገል ፓርቲ እየመሩ የሽግግሩም መሪ ሆነው ኢትዮጵያን ከዴሞክራሲያዊ ተስፋ ማድረስ አይችሉም። ይህን በውስጥ ልቦናቸው ማህደር ጭምር ያውቁታል። ምርጫ ግን አላቸው። በህሊናቸውም፣ በልጆቻቸውም፣ በኢትዮጵያ ህዝብ ፊትም ሆነ፣ በዓለሙ ዐይን ታላቅ ሆነው መገኘትና ሥልጣን ከሚያስከትለው ጭካኔና ፀፀት መራቅ ከፈለጉ በምርጫ የሚወዳደር ፓርቲ መሪነታቸውን ትተው፣ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ሥልጣኑን እንደያዙ ከየትኛውም ፓርቲ ተጠቃሚነት የፀዳ የሽግግር አመራር መስጠት ይችላሉ። ፍላጎታቸው ከሆነም፣ ተደራድረው ከዴሞክራሲያዊ ምርጫው በኋላ የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት ሆነው መቀጠል ይችላሉ። በፕሬዚደንትነታቸውም ወቅት፣ አሁን የጀመሯቸውን ፕሮጀክቶችም ሆኑ፣ ሌሎች የወጠኗቸውን መሥራት ይቻላቸዋል። የተባበሩት መንግስታት ጸሀፊነት ፍላጎታቸውም የሚያይል ከሆነ፣ ኢትዮጵያን በፕሬዚደንትነት ከመሩ በኋላ ቀስ ብለው ይደርሱበታል። ይህ የተሻለው ምርጫ ይመስለኛል።

አንድ ዜጋ ሃገሩን በእርግጠኝነት ከአምባገነንነት ወደ ዴሞክራሲ እንድትሸጋገር ወሳኝ ሚና ከመጫወት በላይ ምን የተሻለ ነገር ሊያደርግላት ይችላል? ይህ በታሪክ ውስጥ በመቶ ዓመታት አንድ ጊዜ የሚመጣ እድል ነው። ይህን ለማየትና ለመጨበጥ ዶክተር አቢይ እውቀቱም፣ ብቃቱም፣ ትህትናውም ይኖራቸዋል ብዬ ለማሰብ እወዳለሁ።

ተጻፈ፣ በዘመነ ኮሮና ወረርሽኝ
ሚያዝያ 16 ቀን 2012 ዓም
**በዝግጅት ክፍላችን የተሰጠ ርዕስ

Click to comment

More in ፓለቲካ

Trending

Advertisement News.et Ad
To Top