Connect with us

በኮሮናቫይረስ ዙሪያ መንግስት ቀጣይ እርምጃዎችን መውሰድ አለበት… ታዋቂ ግለሰቦች

በኮሮናቫይረስ ዙሪያ መንግስት ቀጣይ እርምጃዎችን መውሰድ አለበት... ታዋቂ ግለሰቦች
Photo Facebook

ዜና

በኮሮናቫይረስ ዙሪያ መንግስት ቀጣይ እርምጃዎችን መውሰድ አለበት… ታዋቂ ግለሰቦች

መንግስት የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመግታት በህብረተሰቡ ዘንድ ተጨባጭ ለውጦች እስከሚታዩ ቀጣይ እርምጃዎችን በመውሰድ የዜጎችን ደህንነት መጠበቅ እንዳለበት ኢዜአ ያነጋገራቸው ታዋቂ ግለሰቦች ተናገሩ።

የኮሮና ቫይረስ በቻይና ሁቤይ ግዛት ውሀን ከተማ ከተከሰተ ጊዜ አንስቶ፣ መንግስት በሽታው ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገባ የተለያዩ ጥረቶችን ሲያደርግ እንደነበር ሲገልጽ ቆይቷል።

በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ በቫይረሱ የተያዘ ግለሰብ ኢትዮጵያ ውስጥ ስለ መገኘቱ ካረጋገጠ በኋላ፣ በመንግስት በኩል ጠንከር ያሉ እርምጃዎች መወሰዳቸው ይታወሳል።

ወደ በርካታ አገራት የሚደረጉ የአውሮፕላን በረራዎችን ማስቆም፣ ትምህርት ቤቶችን መዝጋት፣ በርካታ የመንግስት ሰራተኞች ቤታቸው ሆነው እንዲሰሩ ከማድረግ አንስቶ፣ በትራንስፖርት ዘርፍም የተለያዩ ውሳኔዎች ተላልፈዋል።

መንግስት ካወጣቸው መመሪያዎች አንዱ፣ ማህበራዊ ፈቀቅታ በህብረተሰቡ ዘንድ በአግባቡ እየተተገበረ ባለመሆኑ ለበሽታው ስርጭት እድል ይፈጥራል።

በሽታው ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ መከላከል የሚቻለው ርቀትንና ንጽህናን በመጠበቅ መሆኑ ቢገለጽም፣ አንዳንድ ሰዎች ግን ተቀራርበው ሲሄዱ እና የወጡ መመሪያዎችን በኃላፊነት ስሜት ሲተገብሩ አይስተዋልም።

ይህን ተከትሎ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፣ ከታዋቂ ግለሰቦች ጋር የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን በኢትዮጵያ ለመግታት፣ ህብረተሰቡ የባህሪ ለውጥ እንዲያመጣ በመንግስት በኩል ምን አይነት እርምጃዎች ሊወሰዱ ይገባል ሲል ጠይቋቸው ነበር።

የደራሲያን ማህበር ፕሬዚዳንት አበረ አዳሙ፣ ገጣሚ ታገል ሰይፉ እና አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ የኮሮና ቫይረስ በኢትዮጵያ ተዛምቶ የከፋ ጉዳት ሳያመጣ፣ ህብረተሰቡ የባህሪ ለውጥ እንዲያመጣ መንግስት ተመጣጣኝ እርምጃዎችን መውሰድ አለበት ብለዋል።

የደራሲያን ማህበር ፕሬዚዳንት አበረ አዳሙ፣ በሽታው በኢትዮጵያ ከመከሰቱ በፊት ሰለ አስከፊነቱ የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራት፣ በተለያዩ አካላት ሲሰጥ መቆየቱን ተናግረዋል።

በሽታው ከገባ በኋላ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አንስቶ፣ የጤና ሚኒስትር፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች እና የመገናኛ ብዙሃን ስለ በሽታው አስከፊነት በማስተማር የተቻላቸውን ጥረት ማድረጋቸውን ተናግረዋል።

ሁሉም የመገናኛ ብዙሃን ስለ በሽታው አስከፊነት እና መከላከል በሚቻልባቸው መንገዶች እያስተማሩ፣ ባሉበት ርቀትን የመጠበቅ መመሪያ በአንዳንድ ሰዎች እየተተገበረ አለመሆኑ እንዳሳሰባቸው ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ ጎዳናዎች፣ በከፍተኛ የሰዎች ጭንቅንቅ ውስጥ መሆናቸውን ያነሱት ደራሲና ገጣሚ አበረ አዳሙ፣ መንግስት የበሽታውን ስርጭት ለመግታት እና ለመቆጣጠር መመሪያውን በማይተገብሩ ዜጎች ላይ ተገቢውን እርምጃ ሊወስድ ይገባል ብለዋል።

አውሮጳ እና አሜሪካ መቆጣጠር ያዳገታቸውን ይህን አስከፊ በሽታ፣ በኢትዮጵያ ተንሰራፍቶ የበርካቶች ህይወት ከመቅጠፉ በፊት እንቅስቃሴዎችን ሙሉ በሙሉ የመገደብ እርምጃ ሊወስድ ይገባልም ነው ያሉት።

በግጥም ስራዎቹ የሚታወቀው ገጣሚ ታገል ሰይፉ በበኩሉ፣ ሰው በምድር ላይ ሲኖር ለአራት ነገሮች ተገዢ ስለመሆኑ ይናገራል።

አንድ ለህሊናው፣ ሁለት ለይሉኝታው፣ ሶስት ለፈጣሪው፣ አራት ለህግ ተገዢ መሆን እንደሚገባው ያስረዳል።

ለእነዚህ ህጎች ተገዢ መሆን የሰው ልጅ በምድር እስከኖረ ድረስ ግዴታው መሆኑንም ይናራል።

ከቤት አለመውጣት፣ የእጅ ንጽህናን እና ርቀትን መጠበቅ ቀላል የሚመስሉ ነገር ግን ከከባድ በሽታ እራሳችንን እንድንጠብቅ የሚያደርጉ መመሪያዎች ናቸው ይላል።

አሁን ላይ ጊዜው እየረፈደ በመሄዱ፣ መንግስት ከማስተማር ይልቅ ቁጥጥር በማድረግ በዜጎች ላይ አስከፊ የጤና ቀውስ ሳይከትል ወደ እርምጃ ሊገባ እንደሚገባም ነው የተናገረው።

በቴክኖሎጂ ከፍተኛ ደረጃ የደረሱትን አሜሪካ እና አውሮጳ አገራት፣ ልንበልጥ የምንችልበት ቀላል እድል አግኝተናል የሚለው ታገል ሰይፉ፣ የወጡ መመሪያዎችን ተግብረን ኢትዮጵያዊያን ስልጡን ናቸው የሚል እሳቤ ለዓለም ህዝብ ማሳየት አለብን ብሏል።

ኢትዮጵያዊያን ይሄንን ጀብዱ በመፈፀም፣ በአንድ ልብ በመነሳት የወጡ መመሪያዎችን በመተግበር በሽታው የከፋ ጉዳት ሳያስከትል እንዲጠፋ፣ ታሪካዊ ኃላፊነትን ለመወጣት መስራት አለባቸው ብሏል።

የኃይማኖት አባቶች ያላቸው ተሰሚነት ላቅ ያለ በመሆኑ፣ የመንግስት ባለስልጣናት እና አርቲስቶች በመንገድ ወጥተው በሚሰጡት ኮሮናን የመከላከል ቅስቀሳ ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑም ጥሪ አቅርቧል።

የፊልምና የማስታወቂያ ባለሙያው አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ በበኩሉ፣ መንግስት የበሽታውን ስርጭት ለመግታት በርካታ ተግባራት ሲያከናውን መቆየቱን ጥሩ እርምጃ ብሎታል።

እርሱም በቅርቡ በኮሮና መከላከል ዙሪያ፣ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለማስጨበጥ በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች መንቀሳቀሱን ጠቅሶ፣ በህብረተሠቡ ዘንድ በማህበራዊ ፈቀቅታ ረገድ አሁንም ለውጦች አለመምጣታቸውን ተናግሯል።

መንግስት ተጨማሪ እርምጃዎችን ቢወስድ መልካም ቢሆንም፣ ለተወሰኑ ጊዜያት ቤት ቆዩ የሚባል ከሆነም፣ ቤት የሌላቸውንና የእለት ጉርስ የሌላቸውን ዜጎች ከወዲሁ ታሳቢ ማድረግ እንደሚገባ ጠቅሷል።

ህብረተሰቡ የባህሪ ለውጥ በማምጣት ረገድ እየከበደውም ቢሆን፣ ራሱንና ቤተሰቡን ከዚህ አስከፊ በሽታ ለመጠበቅ ሲል የሚወጡ መመሪያዎችን ሁሉ ሊተገብር ይገባልም ብሏል።

(ኢዜአ)

Click to comment

More in ዜና

Trending

Advertisement News.et Ad
To Top